የለጥ ቅዱስ ጊዮርጊስ
ከWikipedia
የለጥ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት፤ በከሰም ወረዳ ውስጥ የሚገኝ ቤተ ክርስቲያን ነው።
ማረጋገጫ ጽሑፍ ባይገኝም፤ አፈ ታሪኩ፣ የጊዮርጊስ ታቦት በቡልጋ የለጥ የተተከለው በዓጼ ዮሐንስ ዘመን ነው ይላል። እስከ 1943 ዓ.ም. ድረስ የቤተ ክርስቲያኑ ሕንጻ ክብ የሳር ክዳን ሕንጻ እንደነበር ይነገራል። እስከ እዚያም ዘመን የሰማእቱ ጊዮርጊስ ታቦት ከማርያም፣ ፋሲለደስ እና መድሃኔ ዓለም ታቦታት ሌላ 13 ታቦታት እዚያው እሳር ክዳን ቤተ ክርስቲያኑ ውስጥ እንደነበሩ ይነገራል።
በ1943 ዓ.ም ንቦች ጣሪያው ውስጥ ሰፍረው ኖሮ ከሳር ክዳኑ ውስጥ ሲገቡ ሲወጡ ይታዩ ነበር። የጊዜውም ካህናት በምስጢር ይሸራረሩኩና ማሩን በድብቅ ለመቁረጥ ይስማማሉ፣ ከዕለታት አንድ ቀን በምሽት ፍም ይዘው ሳር ክዳኑ ላይ ይወጡና ማሩን ቆርጠው ይወርዳሉ፣ ያልተገነዘቡት ግን ፍሙ ለካ እጣራው ወራጅ ላይ ወድቆ ኖሮ አንድ ሳምንት ሙሉ ካፈጋ በህዋላ ተያይዞ ቤተ ክርስቲያኑን ያቃጥለዋል። ቤቱ ሲቃጠል የዋንዛ ዋልታው እመንበሩ ላይ ይወድቃና ታቦቱን ሸፍኖ ቀብሮ ያድነዋል። በየለጥ አካባቢ ሀዘንና ትካዜ ሰፈረ፣ ሕዝቡ ታቦታቱን ሲፈልግ ሰንብቶ በዚያ ጊዜ ከነበሩት 17 ታቦታት ውስጥ የጊዮርጊስ ታቦትና የማሪያም፣ የመድሃኔዓለም፤ የፋሲለደስ ታቦታት ብቻ ሳይቃጠሉ ድነው ተገኙ ይላሉ ቄስ ሰርጸወልድ ተሰማ።
ይኸኔ ልዩ ስምዋ ቡሄ አምባ በምትባለው የየለጥ መንደር በ1907 ዓ.ም ተወልደው በአምስቱ የጣሊያን ዘመን በአርበኝነት ተሰማርተው ሀገራቸውን ያገለገሉት ደጃዝማች ኪዳኔ ወልደመድኅን ቤተ ክርስቲያኑን እንዲያሰሩላቸው ሲጠይቅዋቸው ደጃዝማች ኪዳኔም ቤተ ክርስቲያኑን አሰርተው ከጨረሱ በኋላ ሕንጻው አሰራሩ ቅሬታ ስላሰማቸው አስፈርሰው እንደገና አሰርተው ታቦቱን ሚያዝያ 23 ቀን 1949 ዓ.ም አዲሱ ቤተ ክርስቲያን ሊያስገቡ ቻሉ። ይኼ ቤተ ክርስቲያን በዘማናዊ መልክ በአራት ማእዘን ተሰርቶ በአካባቢው ቡልጋ ውስጥ በቆርቆሮ የተሰራ የመጀመሪያው ሕንጻ ነበር።
በ1995 ዓ.ም ለሚያዝያ ጊዮርጊስ በዓል በተደረገው የሕንጻ ምርመራ ቤተ ክርስቲያኑ አርጅቶ ተሰናጣጥቆ፣ ተበላሽቶ ስለነበር ሕንጻቅን አፍርሶ እንደገና በዘማናዊ መልክ ለማሰራት ተወሰነ። ለዚኽም ሥራ:-
- (ሀ) ገበሬው አሸዋ ከከሰም ወንዝና ከአማሪት ወንዝ፤ ድንጋይ ከልዩ ስሙ በር ከሚባለው ሠፈር ፈንቅለው በሰው ትከሻና በአህያ ሸክም
- (ለ) ሲሚንቶ፤ የሕንጻ ብረት፤ ግንበኞችና ሌላም የሕንጻ ሥራ ባለሙያዎች ከአዲስ አበባ እስከ ሐሙስ ገበያ (አንዳንዴም እስከ ኮረማሽ) ድረስ በጭነት መኪና ተጉዞ ከዚያ በታች (ከኮረማሽ 12 ኪሎሜትር ወይም ከሐሙስ ገበያ 25 ኪሎሜትር) በሰው ሸክምና በአህያ ጭነት እስከ ቤተ ክርስቲያኑ ግቢ ይቀርባል።
- (ሐ) በዚህ ቆላ አካባቢ የውሐ እጥረት ስላለ ከቤተ ክርስቲያኑ በላይ 1.1 ኪሎሜትር ርቀት ያለው ምንጭ ተገኝቶ 3.5 ሜ ስፋት በ 2.0 ሜ ቁመት በ2.0 ሜ ጥልቀት ያለው ማቆሪያ ከተገነባ በኋላ የተጠራቀመውን ውሐ በ ፔትሮል ፐምፕ እየወጣ በላስቲክ ቧንቧ ቤተ ክርስቲያኑ ግቢ ድረስ እየተሳበ ለሥራው አገልግሏል።
አዲሱ ቤተ ክርስቲያን ባለ ስምንት ማእዘን ሕንጻ ሲሆን፤ የመሬቱን ገደላማነት በመጠቀም ግምጃ ቤትና ቢሮ የሚሆን ምድር ቤት ተሰርቶለታል። ሕንጻው ሙሉ በሙሉ በድንጋይ የተገነባ ሲሆን፤ ጣራውን በዘመናዊ ሸክላ መሰል ቆርቆሮ ተደፍኗል። ከአካባቢውም ጋር በቀለም እንዲዋሃድ አረንጓዴ ቀለም ተመርጧል። ደጃዝማች ኪዳኔ ያሰሩት ቤተ ክርስቲያን ተገጥመው የነበሩት የሙገሬ ጽድ መዝጊያና መስኮቶች ከታደሱ በኋላ አዲሱ ቤተ ክርስቲያን ሕንጻ ተመልሰው ሊገጠሙ ችለዋል። ሥራው በሁለት ዓመት ተኩል ተጠናቆ ቅዳሜ ጥቅምት 23 ቀን 2000 ዓ.ም ታቦታቱን አዲሱ ቤተ ክርስቲያን አስገብተናል። በዚህም ዕለት ጸበሉን አስባረክን።
ኢትዮጵያዊ የገጠር ሕዝብ በአንድነት የጋራ ኃይማኖቱን፤ ባህሉንም ሆነ ሰብዓዊ ሕይወቱን የሚኖረው በኃይማኖቱ ማስተናገጃ ቤት ነው። እነሆ በጋራ የዚህን ገጠር ሕዝብ የለጤ እና ሕዝበ ክርስቲያን አስብሎ የሚያስጠራውን የየለጥ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በቅድሚያ ተሰርቶለታል፤ ከዚህ በኋል ትምህርት ቤት፤ ክሊኒክ፤ ወዘተ. ሊከተል ይችላል። ይኼንንና የመሳሰሉትንም ተግባራት ለማስፈጸም እግዚአብሄር ፈቃዱ ይኹን።