ኤላም
From Wikipedia
ኤላም ጥንታዊ ሃገር ነበር። ዛሬ ደቡብ-ምዕራብ ፋርስ በሆነ አቅራቢያ ተገኘ። መነሻው በዋና ከተማው በሱስን (ሹሻን) እና በካሩን ወንዝ ሸለቆ ከታሪክ መዝገብ መጀመርያ ሲሆን እስከ 547 ክ.በ. ድረስ ቆየ። ከሱመር እና ከአካድ (የዛሬ ኢራቅ) ወደ ምስራቅ የሆነ አገር ነበር። የኤላም መንግሥት ለፋርስ ከወደቀ በኋላ ቢሆንም የኤላም ቋንቋ በፋርስ አሐይመንድ መንግሥት በመደብኝነት ቆይቶ ነበር። ይህ ቋንቋ የፋርስኛ ዘመድ ሳይሆን ምናልባት ለደቡብ ሕንድ ድራቪዲያን ቋንቋዎች የተዛመደ ይሆናል።
እስከ ዛሬም ድረስ በፋርስ አገር ውስጥ ኢላም ክፍላገር ከጥንታዊው አገር ተሰይሞ ይገኛል።
ኤላማውያን የራሳቸውን ሀገር ስም ሃልታምቲ ብለው ሰይመውት ሲሆን ለጎርቤቶቻቸው ለአካዳውያን "ኤላም" በመባል ታወቁ። 'ኤላም' ማለት 'ደጋ' ሊሆን ይቻላል። ከዚህ በላይ በብሉይ ኪዳን 'ኤላም' ተብሏል፤ የኖኅ ልጅ ሴም ልጅ ነው።
[ለማስተካከል] የኤላም ጥንታዊ ዘመን
የኤላም መጀመርያ ከተማ ሱስን ወይም ሹሻን ነበር። አንዳንዴም የሱመር አለቆች ወርረው አገሩን ይገዙ ነበር። በሱመር ነገሥታት መዝገብ ዘንድ የኪሽ ንጉሥ ኤንመባራገሲ እንዲሁም የላጋሽ ንጉሥ ኤአናቱምና የአዳብ ንጉሥ ሉጋል-አኔ-ሙንዱ ኤላምን አሸነፉት። በሌሎች ጊዜያት ኤላማውያንም ከተሞች ለምሳሌ የሐማዚ ወይም የአዋን (አቫን) ነገስታት በፈንታቸው ሱመርን ይገዙ ነበር። በአዋን ነገሥታት ዘመን (ክ.በ. 2300 ገደማ) የአካድ ንጉሥ ሳርጐን ኤላምን አሸንፎ ከመግዛቱ በላይ በኤላም ውስጥ አካድኛን ይፋዊ ቋንቋ አደረገበት። ሆኖም በሳርጐን ልጅ-ልጅ-ልጅ በንጉሥ ሻርካሊሻሪ ቀን (ክ.በ. 2240 ገደማ) የአካድ መንግሥት ተሰብሮ ኤላም እንደገና ነጻ ወጣና አካድኛን ተወ። የአዋን መጨረሻ ንጉሥ ኩቲክ-ኢንሹሺናክ ሲገዛ አዲስ ኤላማዊ ጽሕፈት አገባ። ኩቲክ-ኢንሹሺናክ ሹሻንንና አንሻንን በዘመቻ ያዘ። ነገር ግን ከዘመኑ በኋላ ጉታውያን ኤላምን በመውረራቸው የአዋን መንግሥት ጠፋ።
ከመቶ ዘመን ያሕል በኋላ የኡር ንጉሥ ሹልጊ እንደገና ሹሻንን ያዘ። ከዚህ በኋላ የሲማሽኪ ሥርወ መንግሥት በኤላም ተነሣ። በዚህ ወቅት ከመስጴጦምያ ጋር ሰላምና ጦርነት ተፈራረቀና እንኳን ክ.በ. 2030 ገደማ የኡር ንጉሥ ሹ-ሲን ሴት ልጁን ለአንሻን መስፍን በትዳር ሰጠ። ነገር ግን የሱመር ኃይል ደክሞ ይጀምርና ከክ. በ. በ2012፤ በሺማሽኪ ንጉስ በኪንዳታ መሪነት ኤላማውያን ከሹሻን ሕዝብ ጋር ኡር ከተማን አጠፉና ንጉሣቸውን የሹ-ሲን ልጅ ኢቢ-ሲንን ማረኩት። ከዚህ በኋላ ግን የኢሲን ከተማ ንጉሶች ኤላማውያን ከኡር አስወጥተው እንደገና ሰርተውት ኤላማውያን የበዘበዙትን ጣኦታቸውን ናና አስመለሱ።
የሚከተለው መንግሥት (ከ1978 ክ.በ.) 'ኤፓርቲ' ይባላል። ደግሞ ከነገስታት ማዕረግ 'ሱካልማህ' ይባላል። የመሠረተው ንጉሥ 1 ኤፓርቲ ነበር። በዚህ ጊዜ ሹሻን በኤላም ስልጣን ብትሆንም የሜስጶጦምያ ኃያላት እንደ ላርሳ ምንጊዜ ሊይዙት ሞከሩ። 1860 ክ.በ. ገደማ ከሹሻን ወደ ስሜን በሆነ ከተማ የነገሠ ሌላ ኤላማዊ ንጉሥ ኩዱር-ማቡግ ልጁን ዋራድ-ሲን በላርሳ ዙፋን ላይ አስቀመጠ። የዋራድ-ሲን ወንድም ሪም-ሲን ተከተለውና በብዛት ሜስጶጦምያን አሸነፈ።
በዚህ ወቅት በኤፓርቲ መንግሥት ታዋቂ ከሆኑ ነገሥታት መኃል፤ ሺሩክዱቅ የባቢሎንን ሥልጣን ለመቃወም ከሌሎች አገሮች ጋር ስምምነት አደረገ። ሲዌ-ፓላር-ቁፓክ የመስጴጦምያ ነገሥታት እንደ ማሪ ንጉስ ዝምሪ-ሊም እንዲሁም የባቢሎን ንጉስ ሃሙራቢ 'አባት' ብለው ይጠሩት ነበር። ኩዱር-ናሑንተ የአካድ መቅደሶች በዘበዘ። ነገር ግን የኤላም ተጽእኖ በመስጴጦምያ አልቆየም። በ1770 ክ.በ. ገደማ ሃሙራቢ ኤላማውያን አስወጥቶ የላርሳ ንጉሥ ሪም-ሲን ገለበጠውና ሜስጶጦምያን በሙሉ ገዛ። (ሃሙራቢ የዘፍጥረት 14 አምራፌል ሲሆን ዋራድ-ሲን ወይም ሪም-ሲን አርዮክ እንደ ነበር ቢታስብም ዛሬ ብዙ ሊቃውንት ይህን ሃሳብ አይቀብሉም።)
ካሳውያን በ1603 ክ.በ. ገደማ ባቢሎንን ካሸነፉ በኋላ ታሪካዊ ምንጮች አይበዙምና ስለ ኤፓርቲ መንግሥት መጨረሻ ዘመን ብዙ አይታወቅም።
[ለማስተካከል] የኤላም መካከለኛው ዘመን
ከክርስቶስ በፊት ከ1500 ዓመት ጀምሮ በአንሻን ከተማ ዙርያ አዳዲስ ሥርወ መንግሥት ተነሣ። የንገስታት ማዕረግ 'የአንሻንና የሱስን ንጉሥ' ተብሎ ነበር። መጀመርያው 1500-1400 የኪዲኑ ሥርወ መንግሥት ሲሆን የሚከተለው 1400-1210 የኢጊሃልኪ ሥርወ መንግሥት ነበር። ከኢጊሃልኪ 10 ነገሥታት አንዳንዱ ካሣዊ ልዕልት ያገባ ነበር። በ1330 ክ.በ. ገደማ የካሳውያን ንጉስ 2 ኩሪጋልዙ ለጊዜው ኤላምን ወረረ። ከዚያም በ1240 ክ.በ. ገደማ ሌላ ካሳዊ ንጉስ 4 ካሽቲሊያሽ ከኤላም ጋር ሲዋግ አላከናወነም። የኤላም ንጉሥ ኪዲን-ሑትራን በ1232 ክ.በ. የካሳውያን ንጉሥ ኤንሊል-ናዲን-ሹሚ አሸንፎ በ1230 ክ.በ. ደግሞ የካሳውያን ንጉስ አዳድ-ሹማ-ኢዲና አሸነፈ።
የሚከተለው ሥርወ መንግሥት የሹትሩክ ነገሥታት 1210-1100 ያሕል ገዙ። 2ኛው የሹትሩክ ንጉስ ሹትሩክ-ናሑንተ በ1184 ክ.በ. ካሳውይያንን በባቢሎን ሲዋጋ የሃሙራቢ ሕገጋት የተጻፈበትን ድንጋይ ከመማረኩ በላይ የማርዱክና የማኒሽቱሹ ጣኦታትና የናራም-ሲን ሐውልት ወደ ሱስን ማረከባቸው። በ1166 ሹትሩክ-ናሑንተ ካሳውያንን በፍጹም ድል አደረጋቸው። ነገር ግን በ1130 ሱስን ለባቢሎን ንጉሥ ለ1 ናቡከደነጾር ወደቀና የኤላም ንጉሥ ሑተሉሽ-ኢንሹሺናክ ወደ አንሻን ሸሸ። ከሱ በኋላ የኤላም ታሪክ ለጥቂት መቶ ዘመን አይገኝም።
[ለማስተካከል] የኤላም አዲስ ዘመን
ከዚህ ዘመን እስከ 800 ክ.በ. ድረስ ስለ ኤላም ብዙ አይታወቀም። ቢያንስ አንሻን የኤላም ከተማ ሆኖ ቀረ። ኤላም ከባቢሎን ጋር በአሦር ላይ ስምምነት ያደርግ ነበር። የባቢሎን ንጉሥ ማር-ቢቲ-አፕላ-ኡሹር (992-987) ከኤላም ትውልድ እንደ ነበር ይታመናል። ኤላማውያን ከባቢሎን ንጉሥ ከማርዱክ-በላሱ-ኢቅቢ ጋራ ጦርነት በአሦር ንጉስ በ5ኛ ሻምሺ-አዳድ (831-819) ላይ አደረጉ።
በዚህ ጊዜ የማዳይ ሕዝቦች በስሜን ፋርስ ላይ በዝተው ዘመዶቹ ፋርሳውያን ከኡርምያህ ሐይቅ ተነሥተው በአንሻን ዙሪያ ስለ ስፈሩ ኤላማውያን ወደ ሱስን አገር ተገፉ። ሆኖም ለጊዜው የኤላም ነገሥታት ማዕረግ 'የአንሻንና የሱስን ንጉስ' ተብሎ ቆየ። ንጉሥ ሑምባኒጋሽ (751-725) ከባቢሎን ንጉሥ ከመሮዳክ ባልዳን ጋራ በአሦር ንጉስ በ2ኛ ሳርጎን ላይ ስምምነት እንዳደረገ ይታወቃል። ከሱ የተከተለው ንጉሥ 2ኛ ሹትሩክ-ናሑንተ በ718ና በ716 ክ.በ. በሳርጎን ሠራዊት እጅ ድል ሆነ።